Saturday, August 15, 2015

የማለዳ ወግ…ለአሚራና ቤተሰቦቿ የጎደለው ፍትህ … !

Augest 14,2015
Amira
Amira
==================================
* ህጻን የደፋረን የ4 ወር እስር መቅጣት ምን ይሉታል ?
* ፍርዱ ቅጣት ነው?  ወይስ ማበረታታት ?
* ህግ አውጭና አስፈጻሚ አካላት ወዴት ናችሁ?
* ወላጆቿ " ወላጅ ይፍረደን፣ህዝብና ሀገር ይፍረደን!"ይላሉ
የኢፊድሬ ህገ መንግሰት ሴቶች  ልክ  እንደ  ወንዶች  በሕገ-መንግሥቱ  እኩል  መብትና  ጥበቃ  እንዲሰጣቸው ይደነግጋል ትግበራውን መከታተልና ማስፈጸም ያለባቸው ህግ እውጭና አስፈጻሚ አካላት የሴቶችን መደፈር ለመከላከል የከበደ ኃላፊነት እንዳለባቸው ይህው የፈረደበት ህገ መንግስት ያስረዳል  ! ዳሩ ግና አልፎ አልፎ የሚሰማ የሚታየው የነገር ጭብጥ ውጤት ህግ አውጭና የሚያወጡት ህግ ደንብና መመሪያ ከወንጀል ፈጻሚው ባልተናነሰ በህግ አስከባሪና አስፈጻሚዎች ህጉ ይጣሳል ። ህግ ተጥሶ የዜጎች ሰብአዊ መብት መዳጡ  በአደባባይ እየተሰማና እየታየ ህግ አውጭ አካላት የሚወስዱት እርምት እርምጃ አያስደስትም ። የሴት ጠለፋ በተለይም በህጻናትና ታዳጊዎች ላይ የሚፈጸም አስገድዶ  መድፈር ዝርዝሩ ሰፋ ያለ ይሆናል ። ዳሩ ግን የህግ እውቀት ኖሮኝ ያንን ለመተንተን ባይዳዳኝም በህግ አስከባሪዎች ፍትህ እየጎደለ በዜጎች ላይ የሚፈጸመው በደል ዘልቆ ቢያመኝ እንደ ዜጋ በጎደለው ፍትህ ተቃውሞና በቅሬታየ ዙሪያ የዜጋ ድምጼን ማሰማት ግድ ብሎኛል ...
ዛሬ ዛሬ የምንሰማው ሰው በሰው ላይ ቀርቶ በእንስሳ ላይ መፈጸም የሌለበትን ርክሰት የተጠናወተው ወንጀል ጀሯችን ሆኗል ። በተለይ በአቅመ ደካማ ህጻናት ታዳጊዎችና በሴቶች ላይ የሚፈጸመው ወንጀል እያደር መክፋቱ  ጸሀይ የሞቀው እውነት ሆኗል። በዚህ ረገድ እየተኬደ ያለውን የከፋ ወንጀል ሳስበው " ወደ የት እየሄድን ይሆን?  " እያልኩ ያስፈራኛል  ! የአጉራ ዘለል አስገድዶ የመድፈር ወንጀለኞች መስፋፋት ፣ እያደር ውሎ አዳራችንና አብሮነታችን እንዳያጎድፈውም በአስፈሪ የታሪክ ምዕራፍ ላይ እንገኛለን  !  ሴሰኛ ወንጀለኛ ሽምጥ ጋልቦ  እዚህ ሲደርስ ወንጀሉን በጥብቅ ተከታትሎ የማያዳግም ቅጣት አርአያነት ያለው ውሳኔ ቢሰጥ ዛሬ እዚህ ባልተደረሰ ነበር ፣ ይህ አይፈጸምምና ፣ ይህ አልተደረገምና ዛሬ ውርደትን መከናነብ ግድ ብሎናል ።  የተከናነብነው ውርደት ምክንያት የሆነን ወንጀልም ሊሰሙት ከሚችሉት በላይ ሰቅጣጭና የከበደ እየሆነ ለመምጣቱ ብዙ ማሳያዎችን ማቅረብ አይገድም  !
ይህን ሁሉ የምለው በአንዲት የ4 ዓመት ከ6 ወር ብላቴና ተዳጊ ላይ የተፈጸመው ወንጀልና ተመጣጣኝ ያልሆነውን የፍርድ ውሳኔ ወደምቃዎምበት የማለዳ ወጌ የመረጃ ግብአት ለመዝለቅ ነው   ! እንደኔ የፍትህ መዛባት ዘልቆ ያመማችሁ ተከተሉኝና ፍርዱን ስጡ ... !
በያዝነው ሳምንት ማህበራዊ መገናኛ ድህረ ገጾችን ቀልብ የሳበው ጉዳይ መካከል የ4 ዓመት ከ6 ወሯ ታዳጊ  መደፈርን ተከትሎ የተላለፈው ዜና የብዙዎቻችን ቀልብ ስቧል ። ለዚህ መሰሉ ዜና አዲስ ባይንሆንም ብላቴናዋ  መደፈሯ ሳይሰማ ባሳለፍነው ሳምንት ሀሙስ  በመጨረሻ ው የፍርድ ውሳኔ ጋር ሰማን ፣ በውሳኔውም ደፋሪው የ4 ወር እስራት ቅጣት ፍርድ መሰጠቱን በአንድ ላይ ሲነገረን ማመን ከተቸገሩት መካከል አንዱ ነበርኩ።  የጉዳዩን ጭብጥ ለማጣራት ባደረግኩት ሙከራ ያገኘሁት መረጃ ይዠ የዜጋ ተቃውሞ ድምጼን በማለዳ ወጌ ላሰዳ ስውተረተር በድሬ ትዩብ ስሟን በመጥቀስ በጉዳዩ ዙሪያ የቀረበ አንድ ዘገባ ለወጌ መረጃ ግብአትነት ተጠቅሜበታለሁ ። ትክክለኛ ስሟ ስለመሆኑ ግን ማረጋገጫ አላገኘሁም ። ስሟ ቢታወቅም መግለጹ አስፈላጊ ባለመሆኑ የድሬ ትዮብን ስም ተቀብየ እዘልቃለሁ ።  ከዚሁ በተጨማሪ ሌላም ሌላ መረጃዎችን ለማሰባሰብና ለማጣራት ሞክሬ በእርግጥም ወንጀሉ ለመሰራቱና ፍርደ ገምድል ብይን የመሰጠቱ ሁነኛነት አረጋግጫለሁ  !
የተሰራጩ መረጃዎች እንደሚስረዱት ታዳጊዋን የ4 ዓመት ከ6 ወር ተዳጊዋን አሚራ ትባላለች ።  ኑሮዋም አዲስ አበባ አቃቂ ክፍለ ከተማ እንደሆነ ተጠቁሟል። ደፈረ የተባለው አስነዋሪ ወንጀል ፈጻሚ የ25 ዓመት ጎረምሳ ነው። በችርቻሮ ንግድ የሚተዳደሩት የአሚራ ቤተሰቦቿ ቤት ጎን ተከራቶ ነበር አሉ ።
ከውሳኔው አስቀድሞ ተከሳሽ አሚራን ስለመድፈሩ ክስ ቀርቦበት ፣ ጉዳዩ በፖሊስ ቀርቦና ተጣርቶ ተከሳሽ ተይዞ በፊዴራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት የአቃቂ ቃሊቲ ፍርድ ቤት ችሎት የቀረበ ሲሆን በ30 ሽህ ብር ዋስትና ተለቀቀ።  ክሱን በዋስ ወጥቶ እንዲከላከል በፊዴራድ  ከፍተኛ ፍርድ ቤት የአቃቂ ቃሊቲ ፍርድ ቤት ወሰነ ። ያ ከሆነ በኋላ ባሳለፍነው ሳምንት ተከሳሽ  ለብይን ቀረበ ። ፍርድ ቤቱ በፖሊስ የቀረበለትም ምርመራ ተመልክቶ በሰጠው ውሳኔ " ተከሳሽ ድንግልናዋን ባይገስም በእጆቹ የማህጸኗ ግድግዳ የመሰንጠቅና የመላላጥ  ጉዳትና ማድረሱና በማህጸኗ የመቅላት ምልክት በመታየቱ  !" በሚል ማስረጃ  ፍርድ ቤተ ተከሳሽን " ሞከርክ " በሚል ወንጀለኛ ሲል የ4 ወር እስራትን አስተላልፎበታል ። ይህው ፍርድ ቤት ገና የትምህርት ገበታ ያልቀመጠችን ታዳጊ ብላቴና አመራን  የደፈረበትን የጨካኝ ድርጊት ከደፈረ ሞከረ ቀይሮ በቀረበ ማስረጃ በፍትሀ ብሔር ህግ 6264 ሀ መሰረት ውሳኔ መሰጠቱ ተነግሮናል ። አስገራሚ ፣ አስደንጋጭና አሳዛኝ የፍርድ ውሳኔ !
ክሱን አቀለለ ወደተባለው ምክንያት ስንሄድ ደግሞ ይበልጡኑ እንታመማለን ... ወንጀለኛው  " የሳንባ ነቀርሳ በሽተኛና በቀጣዩ አመት ተመራቂ !" መሆኑን በቅጣት ማቅለያነት አቅርቦ በፍርድ ቤቶ ተቀባይነት ማግኘቱ አገኘ ብለውናል  ። ለእኔ  የክስ ማቅለያ የቀረበው ሀሳብ የተማረ የተመራመረው " የዩኒቨርሲቲ ተማሪ " ነኝ ባይ ወንጀለኛ ነው ፣  ምንም የማታውቅን እምቦቃቅላ ታዳጊ ገላን በአሻው መንገድ አድርጎ ገፎታል ፣ ገፈፋውም የተፈጸመው በአንድ አዋቂ መሆኑ ብቻ ወንጀሉን ሊያከብድ እንጅ ሊያቀል ባልተገባ ነበር ባይ ነኝ ። ይህ ያቀረበው የክስ ማቅለያ ይልቁንም በሰነድ ተረጋግጦ ክሱን ማጠንከር ሲገባው ክሱን ማቅለያ ሆኖ መቅረቡና ከምን ወደ ምን እንደቀለለ ያልተገለጸው ማቅለያ ተቀባይነት ማግኘቱ በራሱ  በምንም ሚዛን ፍትሃዊነት የለውም  ! ይህን ለመናገር ሰብእናና የራስን ፍርድ መስጠት እንጅ ግዴታ ህግ ማጥናት አያስፈልገውም ...
የህዝብን መብት ለማስጠበቅ የተሰየሙትን የፍትህ አካላት የሙያ ብቃት ጥያቄ  ውስጥ የጣለው ይህ መሰሉ አሳዛኙ የፍትህ ውሳኔ ማህበረሰቡ በፍትህ እንዳይተማመን ከማድ ረግ ባሻገር በህግ ጥላ ስር መጠበቁን በጥርጣሬና እንዲ ያይ እንደሚያደርገው ጥርጥር የለኝም ። ከዚህም አልፎ ተርፎ በአሚራ ደፋሪ ላይ የተላለፈው ውሳኔ ሀገሬው  ፍትህ አጥቶ የሚንገዋለል እንዲሆን አድርጎታል ወደሚል መደምደሚያ አድርሶኛል ... የአስገድዶ መድፈር ወንጀለኞ ች ጉዳይ መስፋፋትና ገደብ ማጣት በተደጋጋሚ በመንግ ስት ላይ የሰላ ወቀሳ ይቀርባል ። በተለይም የህግ ጥበቃ ውንና ቅጣቱን ከማጠንከሩ በተጓዳኝ ተማኝነት እንጅ የሙያ ብቃት ሚዛን ሆኖ ቅጥር ስለማይፈጸም ተደጋጋሚ ችግሮች ተስተውለዋል ። የፍትህ አካላት ብዛት እንጅ ጥራት የጎደላቸው መሆኑ ከዚሁ ጋር ይጠቀሳል ።  የተባለውን ወቀሳ እውነታነት እንዳለው ለመረዳት የአሚራን አይነት በደል ተሰርቶ የተሰጠውን ውሳኔ መመልከት ብቻ  ማየት ከበቂ በላይ ይመስለኛል  ።
በአሚራ ውሳኔ አሰጣጥ  እንዳየነው ከምንም በላይ የፍትህ ስርአቱ በወንጀለኛውም ሆነ በጠበቆች የቀረበውን የተውተፈተፈ መከላከያና ቅጣት ማቅለያ መቀበላቸው ለፍትህ አካላት የደረሱበትን ደረጃ ያሳይ ከሆነ መልካም ነው ። የአሚራን ጉዳይ በግርድፉ ላየ ለተመለከተው   ጥፋታቸውን በአዞ እንባ ለመሸፋፈን ከተጉ ወንጀለኞች ጎን ለገንዘብ ብለው ጥፋቱን ለማቅለል ሚሞግቱት ጠበቆች ሰብዕና ያማል ፣  የዳኞቹ ውሳኔ አሰጣጥና ውሳኔ ማቅለያ አቀባበል ደግሞ  ይገርማል ፣ ይደንቃል ... !  ይህ መሰል ከእውነታው ጋር የሚጋጭ የተፋለሰ ፍርድ  በአደባባይ ሲሰጥ ህጉን ማስከበር ያለባቸው አቃቤ ህግ ተወካዮች የታሉ  ? ፍትህ ወዴት ነህ  ?  ያስብላል ...
በሰብዕና ላይ ወንጀል ሲሰራ በቸልተኝነት መመልከት ሊቆም ይገባል ።  የሴቶችን መብት ለማስከበር ተብሎ የወጡት ሕጎች  ተፈጻሚ  ይሆኑ ዘንድ  የኢትዮጵያ  ሰብአዊ  መብት  ኮሚሽን  አካል  የሆነ  የሴቶችና ሕጻናት  ጉዳዮች  ብሔራዊ  ኮሚሽንን  በ2005  ዓም መቋቋሙን ከሰማን አመታት ተቆጥረዋል ።  ኮሚሽኑ በሴቶችና  በሕጻናት ለሚፈጸሙ የሰብአዊ  መብት  ጥሰት  ተገን እንደሚሆን ቢጠቀስም ለአሚና የጎደለ ፍትህ ድምጹን ሲያሰማ አለመታየቱ ግር ያለው እኔን ብቻ ከሆነ መልካም ነው ፣ ግን አይመስለኝም ። " መብቷ ይከበር ፣ ፍትህ ጎድሎባታል፣  ፍትህ ታግኝ " የምንላት  ታዳጊዋ አሚራ ያለ ፈቃዷ አይደለም ገላዋ የጸጉር መጠምጠሚያ "ሂጃቧ " ሊነካ አይገባም ፣ ከተነካ ህግ ተጥሷል ! አሚና ድንግልናዋ አልተገሰሰም ፣ ማህጸኗ ግን ተነካክቷል ብሎ ወንጀለኛን ከአስገድዶ መድፈር ወንጀል ማራቅ ፣ ማሸሸት ፍትህን ማረጋገጥ ሳይሆን ፍትህን ማርከስ አድርጌ ነው የምቆጥረው ።  ወንጀለኛው " አስገድዶ የደፈረ " ለመባል አሚራ በጭካኔ ተደፍራ እንደተገደለችው እንደ ሀና ኦላንጎ መሆን አልነበረባትም  ! አሚራም ሀና እንደሆነችው ባትሆንም በአሚራም ማህጸን ዙሪያ ክብረ ነክ የመድፈር ሙከራ አድርጓል ። የቀረበው ማስረጃ የሚየስረዳው አርቆ አሳቢው የተማረ ጎልማሳ ምንም በማታውቀው የ4 ዓመት ከ6 ወር ታዳጊ ህጻን ላይ ወንጀል አስገድዶ መድፈር ለመሆኑ ሌላ ከበቂ በላይ ማስረጃ  አለ ብየ አላምንም!
የሴቶችና ሕጻናት  ጉዳዮች  ብሔራዊ  ኮሚሽንን  ሴቶች  ሥርዓተ-ፆታን  መሠረት  ያደረገ  ጥቃት ደርሶባቸው እንዲህ ሲመለከት አብሮ ከተጎጅ ወገኖች ጎን  መቆም ፣ የሕግ  ጥበቃ  ማቆም ፣ የህግ ጠበቃ የማቆም አቅም ከሌለው  የህግ ጥሰቱን በአደባባይ ተቀውሞ ስታዳጊዋ ብላቴና ስለአሚራ ፍትህ ማግኘት ድምጹን ሊያሰማ ይገባል !
በፍርድ ገምድሉ ውሳኔ ያዘኑ ቤተሰቦች  ወላጆቿ ፍትህ ጎድሎባቸው " ወላጅ ይፍረደን፣ህዝብና ሀገር ይፍረደን!" ማለታቸው ስሰማ የእነሱም ጩኸትና አቤቱታ የእኔም ለአሚራና ቤተሰቦቿ ፍትህ ርትዕ ይከበርላቸው የሚል ጥያቄ እንዳነሳ አድርጎኛል  ! ከምንም በላይ የሴት ልጅ በረከት የታደልኩ አባት እንደመሆኔ የሴት ልጅን ወሰን የሌለው ፍቅር አውቀዋለሁና ከአሚራ ቤተሰቦች ጋር ልቤ በሀዘን ተሰብሯል ፣ በጎለው ፍትህ አምርሬም አዝኛለሁ ... !
ፍትህ ለህጻን አሚራና ቤተሰቦቿ ስል እጠይቃለሁ  !
ነቢዩ ሲራክ
ነሀሴ 5 ቀን 2007 ዓም

No comments: